የሀገር መከላከያ ሰራዊትና የፌዴራል ፖሊስ ከክልሎቹ የጸጥታ ሀይሎች ጋር በመሆን በወሰዱት እርምጃ በቁጥጥር ስር መዋሉን መንግስት አስታወቀ

ባለፉት ሁለት ቀናት በኦሮሚያ እና የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች አዋሳኘ አካባቢዎች የተፈጠረው ግጭት በኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ትእዛዝ የሀገር መከላከያ ሰራዊትና የፌዴራል ፖሊስ ከክልሎቹ የጸጥታ ሀይሎች ጋር በመሆን በወሰዱት እርምጃ በቁጥጥር ስር መዋሉን መንግስት አስታወቀ።
የመንግስት የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሀላፊ ሚኒስትር ዶክተር ነገሪ ሌንጮ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንዳሉት፥ ከትናንት በስቲያ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሀረርጌ ደደር ወረዳ ሁለት አመራሮች መገደላቸውን ተከትሎ ግጭት መቀስቀሱን፤ ይህም ወደ አወዳይ በመዛመት በሁለት ቀን ውስጥ የሰው ህይወት ሲጠፋ በንብረት ላይ ውድመት አስከትሏል።
ችግሩ ከመባባሱ ጋር ተያይዞ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ በተሰጠው ትእዛዝ የፌደራል ፖሊስ ከኦሮሚያ እና ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች የጸጥታ ሀይሎች ጋር በመሆን ግጭቱን ማርገብ መቻሉን ነው ያመለከቱት።

የፌደራል ፖሊስ እንዲሁ ወደ አካባቢው ገብቶ ትጥቅ እንዲያስፈታ በማድረግ በሰው እና ንብረት ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ቁጥጥር በማድረግ ላይ ይገኛልም ብለዋል።
ሀላፊ ሚኒስትሩ፥ በሁለቱ ክልሎች አዋሳኝ ላይ ቀደም ብሎ ይፈጠር የነበረውን የመሬት ይገባኛል ጥያቄ በክልሎቹ ስምምነት መሰረት በህዝበ ውሳኔ ስምምነት ተፈጥሮ የማካለል ስራ እየተከናወነ ነው።
ይሁን እንጂ ከሳምንት በፊት በሞያሌ አካባቢ ግጭቶችን ለማስነሳት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች በመታያቸው የክልሎቹ ርእሰ መስተዳድሮች ከሚመለከተው የፌደራል መንግስት ተቋም ጋር በመሆን ችግሩ ሳይፈጠር ማስቆም ተችሏል።
ነገር ግን ከትናንት በስቲያ ደደር ወረዳ አካባቢ የተነሳው ግጭት ወደ አወዳይ ተዛምቶ ከጠፋው የሰው ህይወት እና ንብረት በተጨማሪ 600 የሚሆኑ ሰዎች ከሁለቱ ወረዳ ተፈናቅለው እስከ ትናንት ሀረረ ከተማ ላይ ቆይተው ዛሬ ላይ ችግሩን መቆጣጠር በመቻሉ ወደ አከባቢያቸው እንዲመለሱ እየተደረገ ነው ያሉት።
ከዚህ ጎን ለጎን በሂደቱ የሰብአዊ መብት ጥሰት ይኑር አይኑር የሚለውንም ለማጣራት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እንዲያጣራ በተሰጠው ትእዛዝ መሰረት ስራውን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ለማወቅ ችለናል።
ሚኒስትሩ ዶክተር ነገሪ ሌንጮ በመጣራት ላይ ያሉ መረጃዎች ሲጠናቀቁ ይፋ እንደሚደረጉ በመግለፅ፥ በሚገኘው ውጤት መሰረት ተጠያቂዎችን በመለየት ለህግ እንዲቀርቡ ይደረጋል ብለዋል።
ችግሩ በሰው ህይወት እና በንብረት ላይ ጉዳት ሳያደርስ መከላከል በሚቻልበት ሁኔታና የፌደራል መንግስት ጣልቃ ለመግባት አልዘገየም ወይ ለሚለው ጥያቄም፥ ሚኒስትሩ ከሁለቱ ክልሎች ጋር ቀድሞ መነጋገር በማስፈለጉ እንደሆነ እና ይህንንም ተከትሎ ትእዛዙ ተላልፎ ወደ እርምጃ ተገብቷል ብለዋል።
በክሎቹ ወሰን አካባቢ የሚፈጠሩ ችግሮችን ለመፍታት ቀድሞ የተጀመሩት የመፍትሄ አቅጣጫዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ያነሱት ሚኒስትሩ፥ ዳግም እንዲህ አይነት ችግሮች እንዳይከሰቱ ቅንጅታዊ ስራውን የማጠናከር ተግባር ትኩረት ይሰጠዋል ብለዋል።

source:FBC

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

Ministiroota Itiyoophiyaa har'a muudaman

Ibsa Dhaabbatummaa Dh.D.U.O

Obbo Muktaar Kadir pireezidaantii Mootummaa Naannoo Oromiyaa ta’uun lammata filataman