ዳግማዊ ጥልቅ ተሃድሶው የእነ ቶሎ ቶሎ ቤት…. እንዳይሆን

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ጥልቅ ተሃድሶ በመካሄድ ላይ እንዳለ ይታወቃል።ተሃድሶ ሂደት እንደሆነና በአንድ ወቅት የማይጠናቀቅ መሆኑ ሲነገርም ይሰማል፤እውነት ነው ተሃድሶ በሂደት ከግቡ መድረስ የሚችል መሆኑ ላይ ሁሉም ወገን መግባባት መቻል አለበት ነገሩ የእነ ቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ አይነት መሆን የለበትም

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በማካሄድ ላይ የሚገኙትን ጥልቅ ተሃድሶ ላይ ተመስርተው የአመራር ለውጥ በማድረግ አዳዲሶቹን አመራሮች ለተገልጋዩ ሕዝብ አስተዋውቀው ይፋ አድርገዋል መልካም ነው
ነገር ግን በግንባሩ አባል ድርጅቶች ውስጥ እስከ አሁን በየደረጃው የተደረገው የአመራር ለውጥ ከፍና ዝቅ ያለበት ሁኔታ ታይቶበታል፤በዚህ ረገድ የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት(ኦህዴድ) የወሰደው እርምጃና በየደረጃው ያካሄደው የአመራር ለውጥ የተሻለ እንደሆነ ብዙዎች ይናገራሉ
ስለዚህ ቀደም ሲል የተካሄደው የሌሎች እህት ድርጅቶች የተሃድሶ እንቅስቃሴና በአመራሮች ላይ የተወሰደው እርምጃ ለምን ከኦህዴድ ያነሰ ሆኖ ተገኘ?ብለው የሚጠይቁ ወገኖች አሉ የጥያቄው መነሻ የኦህዴድ ሊቀመንበር አቶ ሙክታር ከድር እና ምክትል ሊቀመንበሯ ወይዘሮ አስቴር ማሞ ሙሉ በሙሉ ከሃላፊነታው መነሳታቸው ነው፤ከዚህም ሌላ በኦሮሚያ ክልል በተለያየ ደረጃ በአመራር ላይ የነበሩ በርካታ ሰዎች በአዲስ ተተክተዋል፤ቀሪዎቹም ከነበሩበት የሃላፊነት ቦታ ወደ ሌላ እንዲዛወሩ ተደርጓል ይህም መልካም ነው
ነገር ግን በዋናነት የስርአቱ አደጋዎች ናቸው ተብለው የተለዩት ችግሮች  የጥበትና ትምክህት(ጥገኝነት) አመለካከቶችና ድርጊቶች፤ኪራይ ሰብሳቢነት፤አክራሪነት፤ስልጣንን ለግል ኑሮ ማደላደያ አድርጎ መጠቀም በሕወሃት፤በብአዴንና በደኢህዴን ሰዎች ውስጥ የነበረው የስርአቱ አደጋ በጥቂቱ ነው ያለው ማለት ነው? በኦህዴድ ሰዎች ውስጥ የነበረው የስርአቱ አደጋ ሲሰፈር መጠኑ ምን ያህል ይሆን?
ኢህአዴግ ይህን ጉዳይ በአግባቡ ማጤን ይጠበቅበታል፤ምክንያቱም የኢህአዴግ ህልውና በአራቱ ብሄራዊ ድርጅቶች እኩልነት ላይ የተመሰረተ ነውና።በእኩልነት ላይ ሳይመሰረት የሚወሰድ እርምጃ ሌላ አስከፊ ችግር እንዳይወልድ ያሰጋል በቅርቡ በየክልሎቹ በተወሰዱ እርምጃዎች በተግባር የታዩት መዛነፎች  የህዝብ ጥቆማዎችን መሰረት በማድረግ በአጥፊዎች ላይ በሚወሰዱ እርምጃዎች ይስተካከላሉ የሚል ተስፋ አለ
ሰሞኑን በዴሞክራሲ ማዕከል የገጠር ዴሞክራሲ ማስተባበሪያ ሃላፊ ሆነው በቅርቡ የተሾሙት አቶ ተፈራ ደርበው በሰጡት ማብራሪያ በቀጣይ ከሕዝብ ጋር በሚደረገው የተሃድሶ ውይይት ህብረተሰቡ በሚያቀርበው ጥቆማ መሰረት የተደበቁና ያልታዩ ጉዳዮች ተለይተው እርምጃ ይወሰዳል ብለዋል፤ለዚህ ስኬትም ህበረተሰቡ ያለምንም መሸፋፈን ጥፋተኞችን ማጋለጥ እንደሚጠበቅበት አቶ ተፈራ ደርበው ጥሪ አቅርበዋል
በሕዝብ ጥቆማዎች ላይ በመመስረት ጥፋተኛ ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ ሃላፊዎችን ተጠያቂ ለማድረግ ካላቸው ንብረት ጋር ተያይዞ በዘመድ አዝማዶቻቸው ላይ ጭምር ፍተሻ የሚደረግ መሆኑ ተነግሯል
እዚህ ላይ ከአመታት በፊት በፌዴራልና ክልሎች የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽኖች የተመዘገበው የባለስልጣናትና ተሹዋሚዎች ንብረት ለአመታት ከሕዝብ ተደብቆ የቆየ ቢሆንም አሁን ያለምንም መሸፋፈን ይፋ የሚደረግበት ሁኔታ ተመቻችቷል ማለት ይቻላል፤ ነገር ግን ተጨባጭ ተግባር ይጠበቃል።
ከባለስልጣናትና ተሹዋሚዎች ንብረት ምዝገባና ማሳወቅ ጋር ተያይዞ በተለያዩ ወቅቶች የተመዘገበውን የባለስልጣናትና ተሹዋሚዎች ንብረት ለሕዝብ ላለማሳወቅ በሚዲያዎች ሲጠየቅ የተለያዩ ምክንያቶችን በመደርደር ወገቤን ሲል የቆየው የፌዴራል ስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አሁን ሳይወድ በግድ የመዘገበውን ለሕዝብ ይፋ የሚያደርግበት ሁኔታ ተፈጥሯል
ሕዝብ አጥርቶ የሚያይ ዓይን አለው
በኢህአዴግ ውሳኔና በሕዝባዊ አመፅ አስገዳጅነት ምክንያት ከጥቂት ወራት በፊት ተጀምሮ በመካሄድ ላይ ያለው ሁለተኛው ጥልቅ ተሃድሶ ከኢህአዴግ አባል ድርጅቶች አመራሮችና መላ አባላት አልፎ ወደ ሰፊው ሕዝብ  የሚዘልቅበት ሁኔታ ተመቻችቷል፤በየአካባቢው በሚካሄዱ የተሃድሶ የውይይት መድረኮች ላይ ህብረተሰቡ እንዲሳተፍ ጥሪ እየተደረገ ነው፤ለአገሩ እድገትና ልማት የሚቆረቆር ዜጋ ሁሉ በእነዚህ የውይይት መድረኮች ላይ በመሳተፍ ሙሰኞችን ማጋለጥ ይጠበቅበታል
የሕዝብ አይን ሁሉንም ነገር አጥርቶ ማየት የሚችል ነውና ከሕዝብ ዓይን ሊደበቅ የሚችል ምንም ነገር ሊኖር አይችልም፤የሕዝብ አይን የትኛውም ባለስልጣን የተሰጠውን ስልጣን ለግልና በአካባቢው ለሚገኙ ግለሰቦች ጥቅም ማዋል አለመዋሉን፤ከደመወዙ አቅም በላይ መኖሩን፤ማን ግዙፍ ሕንፃ እንደገነባ፤በዘመድ አዝማዱ ስም የሕዝብና የመንግስትን ገንዘብና ንብረት ዘርፎ የራሱ ህጋዊ ሃብት ማን እንዳስመሰለ ሰፊው ሕዝብ ያውቃል

“ብዙ እናውቃለን ብንናገር እናልቃለን” አሁን በፍፁም አይሰራም ሁሉም የሚያውቀውን መናገር መቻል ይጠበቅበታል።ሕገ ወጦችን የማጋለጡና ተጠያቂ የማድረግ ስራ የኢህአዴግ መዋቅር ተግባር ብቻ መሆን የለበትም፤በኢህአዴግ መዋቅር ውስጥ በተለያዩ ምክንያቶች የተሰገሰጉ ሌቦችና ሕገ ወጦች ተጋልጠው ተጠያቂ መሆን የሚችሉት ሕዝብ በማጋለጡ ስራ ላይ ያለምንም ማቅማማት መሳተፍ ሲችል ነው፤የሕዝብ አይን ሁሉንም ነገር አጥርቶ ማየት የሚችላልና አሁን ተራው የሕዝብ ነው።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

Ministiroota Itiyoophiyaa har'a muudaman

Ibsa Dhaabbatummaa Dh.D.U.O

Obbo Muktaar Kadir pireezidaantii Mootummaa Naannoo Oromiyaa ta’uun lammata filataman