መካከለኛ አመራሩ ለህዝብ ጥቅም በፅናት መቆም አለበት

በኦሮሚያ ክልል በየደረጃው የሚገኙ አስፈጻሚ አካላት የግል ጥቅማቸውን ከማስቀደም ተቆጥበው የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንዲረባረቡ የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት/ኦህዴድ / ምክትል ሊቀመንበር ዶክተር ወርቅነህ አሳሰቡ።

ላለፉት ስምንት ቀናት በአዳማ ከተማ ሲካሄድ የቆየው የመካከለኛ አመራሮች ጥልቅ የተሃድሶ መድረክ ትናንት ተጠናቋል።

በመድረኩ ማጠቃለያ ላይ የተገኙት የኦህዴድ ምክትል ሊቀመንበሩ ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓቱን ከሚፈታተኑት ችግሮች መካከል አንዱ የመንግሥት ሥልጣንን የሕዝቡን ኑሮ ለማሻሻልና ለውጡን ለማስቀጠል እንዲሆን ከማድረግ ይልቅ የግል ኑሮን መሠረት አድርጎ የመመልከትና የግል ጥቅም ከማስቀደም ጋር የተያያዘ መሆኑን አመልክተዋል።

በተለይ በየጊዜው ከሰፊው ህዝብ ጋር በቀጥታ የሚገናኙ መካከለኛ አመራሮች ችግሩ የሚያስከትለውን አደገኛ ውጤት በውል ተገንዝበው ከማናቸውም የግል ጥቅም በጸዳ አግባብ የህዝብን ጥቅም ማዕከል አድርገው በመስራት የድርጅቱን ተልእኮ በአግባቡ እንዲወጡም አሳስበዋል።

"ይህንን ለማስፈን ጠንካራ ትግል ይጠይቃል " ያሉት ምክትል ሊቀመንበሩ ከዚህ ችግር ለመላቀቅ ሁሉም ከአሁኑ መዘጋጀትና መወሰን እንዳለበት ነው የተናገሩት።

"በአሁኑ ወቅት ህዝቡ ከእኛ የሚፈልገው የበደልነውን ለመካስ በቁርጠኝነት ተነሳስተን የሚታይ ተጨባጭ ስራ መስራት ብቻ ነው" ብለዋል።

ከህዝብ የቀረቡ የልማት ጥያቄዎች በአግባቡ ምላሽ ማግኘታቸው በተጨባጭ ለማረጋገጥ አመራሩና አስፈጻሚው አካል ህዝቡን ቀርቦ የተከናወኑ ስራዎችንና የመጡ ለውጦችን ማሳየትና መተማመንን መፍጠር ህዝቡ ከምንም በላይ የሚፈልገው ጉዳይ መሆኑን ጠቁመዋል።

ዶክተር ወርቅነህ ከዚህ ውጪ ማንም አካል በቅንነትና በታማኝነት ሳይሰራና ሳያገለግል እንደ ድሮ ህዝብ ፊት መቆም አይችልም ነው ያሉት።

ይህንን በእምነት ተቀብሎ ለህዝብ ጥቅም፣ ዕድገትና ብልጽግና በቁርጠኝነት መስራት የዚሁ አመራር ኃላፊነት ሊሆን እንደሚገባም አሳስበዋል።

በቀጣይ በመልካም አስተዳደር ረገድ የሚስተዋሉ ችግሮችን አንድ በአንድ በማንሳት ለመፍታትና ወጣቱን ወደ ስራ ለማስገባት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥተው መስራት ይጠበቅባቸዋል፡፡

አገልግሎት ፈልጎ ወደ መንግስት ተቋም የሚመጣውን ህብረተሰብ ከወንበር በመነሳት ጭምር ምን ላግዝህ ብለው በቅንነት በማገልገል አርአያ እንዲሆኑም ጠይቀዋል።

እንደ ዶክተር ወርቅነህ ገለፃ አመራሩ ይህንን ተልዕኮ መወጣት ከቻለ ድርጅቱን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግና ዳግም አዲስ ታሪክ እንዲሰራ ያስችለዋል።

የተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴና እንደገና የመታደስ ጥረት ለላቀ ፍሬ እንዲበቃ መላ የድርጅቱ አባላትና ሕዝቡ በየደረጃው ትግላቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ምክትል ሊቀመንበሩ ጥሪ አቅርበዋል።

የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው ችግሮቻቸውን ለመፍታት የማያዳግም እርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀታቸውን ባወጡት የጋራ አቋም መግለጫ አረጋግጠዋል።

ከህዝቡ በተነሱ ቅሬታዎችና ትችቶች ዙሪያ በጥልቅ መታደሳቸውን ገልጸው ህዝቡን መሠረት ያደረጉ የመልካም አስተዳደርና የልማት አጀንዳዎችን ከህዝቡ ጋር በቅርበትና በብቃት ለመወጣት መወሰናቸውንም አስታውቀዋል።

በመድረኩ ላይ ከሰሜንና ምስራቅ ሸዋ፣አርሲ፣ምዕራብና ደቡብ ምዕራብ ሸዋ፣ፊንፊኔ ልዩ ዞንና በዙሪያው ያሉ ከተሞች እንዲሁም ከአዳማ፣ ከክልል ቢሮዎችና በፌደራል ደረጃ የሚሰሩ መካከለኛ አመራሮች መሳተፋቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

Ministiroota Itiyoophiyaa har'a muudaman

Ibsa Dhaabbatummaa Dh.D.U.O

Obbo Muktaar Kadir pireezidaantii Mootummaa Naannoo Oromiyaa ta’uun lammata filataman