በስም ማጥፋት ተግባር ውስጥም ሆነ በሌሎች አላስፈላጊ ጉዳዮች እየተሳተፉ የሚገኙ ዕድሜያቸውን ለማሳጠር እየጣሩ ያሉ አካላት ናቸው››

‹‹በስም ማጥፋት ተግባር ውስጥም ሆነ በሌሎች አላስፈላጊ ጉዳዮች እየተሳተፉ የሚገኙ ዕድሜያቸውን ለማሳጠር እየጣሩ ያሉ አካላት ናቸው››

ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር)፣ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ
በመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤትና በሚኒስትሩ ላይ የስም ማጥፋት ዘመቻ የከፈቱ ባለሥልጣናትም ሆኑ ግለሰቦች፣ ዕድሜያቸውን ማሳጠር የፈለጉ ናቸው ሲሉ ሚኒስትሩ ነገሪ ሌንጮ (/) ተናገሩ።
ሚኒስትሩ ይህንን የተናገሩት ሰኞ ኅዳር 11 ቀን 2010 ዓ.ም. የበጀት ዓመቱን የሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸምና ቀጣይ ዕቅድ ለምክር ቤቱ የባህል፣ ቱሪዝምና መገናኛ ብዙኃን ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሲያቀርቡ ነው።
ሚኒስትሩ ስለገጠማቸው የስም ማጥፋት ዘመቻ ለቋሚ ኮሚቴው ባቀረቡት ሪፖርት ውስጥ ያካተቱት ነገር ባይኖርም፣ የኮሚቴው አባላት ግን በጽሕፈት ቤቱና በሚኒስትሩ ላይ እየተፈጸመ ነው ስላሉት የስም ማጥፋት ዘመቻ በጥያቄ መልክ አቅረበውላቸዋል። የቋሚ ኮሚቴውና የፓርላማው አባል አቶ ወንድወሰን መኮንን በኢሕአዴግና በኢሕአዴግ ድርጅቶች ጥላ ሥር ሆነው ጎጠኝነትና ዘረኝነትን የሚያስፋፉ፣ በጽሕፈት ቤቱና በሚኒስትሩ ላይም የስም ማጥፋት ዘመቻ እየፈጸሙ መሆኑን ተናግረዋል።
‹‹እንደ አገር እናስብ ካልን የሚጠቅመን ኢትዮጵያዊነታችን እንጂ ዘረኝነትና ጎጠኝነት አይደለም፤›› ያሉት የምክር ቤቱ አባል፣ ‹‹ኢሕአዴግን ተጠልለው እንዴት ነው ዘረኝነትን በኦፊሴላዊ ደረጃ የሚያራምዱት?›› ሲሉ ጠይቀዋል።
ጽሕፈት ቤቱን ያቋቋመውም ሆነ ሚኒስትሩን የሾመው ፓርላማው እንደሆነ በማስታወስም፣ አስፈላጊ ከሆነ የመንግሥት ኮመዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤትን ሥልጣንና ኃላፊነት በድጋሚ ሊደነግግ ይገባል ብለዋል። በማከልም፣ ‹‹ተቋሙም ሆነ ሚኒስትሩ የሚወክሉት መንግሥትን፣ የሚያንፀባርቁትም የመንግሥትን አቋም ስለመሆኑ ሁሉም ወገን ሊገነዘብ ይገባል፤›› ሲሉ በአጽንኦት ተናግረዋል።
ይኼንን ጉዳይ በተመለከተ በሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸው ያላካተቱት ሚኒስትሩ ቋሚ ኮሚቴው በጉዳዩ ላይ ላሳየው ተቆርቋሪነት ምስጋናቸውን ችረዋል። በሰጡት አስተያየትም፣ ‹‹በስም ማጥፋት ተግባር ውስጥም ሆነ በሌሎች አላስፈላጊ ጉዳዮች ውስጥ እየተሳተፉ የሚገኙ ዕድሜያቸውን ለማሳጠር እየጣሩ ያሉ አካላት ናቸው። ብዙ ርቀት ይሄዳሉ ብዬ አላስብም፤›› ብለዋል።
የሚመለከተው አካል ግምገማ አድርጎ ዕርምጃ ይወስዳል ብለው እንደሚጠብቁም ተናግረዋል። በኦሮሚያ የተለያዩ አካባቢዎች የነበሩ ተቃውሞዎችንና ግጭቶችን የብሔር ግጭት መልክ እንዳለው አድርገው የዘገቡ የሚዲያ ተቋማትን ሚኒስትሩ ማውገዛቸውና ሕጋዊ ዕርምጃ እንዲወሰድባቸው ከሚመለከተው ተቋም ጋር መነጋገራቸውን አስመልክቶ መግለጫ በሰጡ ማግሥት፣ ሚኒስትሩ የሰጡት የግል አስተያየታቸውን ነው መባሉና ይህም በተለያዩ የሚዲያ ተቋማትና የማኅበራዊ ትስስር ድረ ገጾች በስፋት መሠራጨቱ፣ የሚኒስትሩን ሥልጣን እንዳሳነሰና የስም ማጥፋት ዘመቻም እንደሆነ በመቆጠሩ ነው የቋሚ ኮሚቴውም መወያያ ሊሆን የቻለው።
 የሚኒስትሩን መግለጫ የግል አስተያየት ሊሆን ይችላል ያሉት የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዘርዓይ አስገዶም መሆናቸው ይታወሳል። አቶ ዘርዓይ ይኼንን ያሉት በአገሪቱ ሕግ መሠረት ሚዲያዎችን የመቆጣጠርና የመቅጣት ሥልጣን በዋናነት እርሳቸው የሚመሩት ተቋም፣ በመቀጠል ደግሞ የፍርድ ቤቶች መሆኑን ሲያብራሩ ነው። ወቅታዊ የፖለቲካ ቀውሶችን ሚዲያዎች በሚዘግቡበት ጊዜ ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በይፋ አሳስበውና ይህንንም ማሳሰቢያ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን አጽንኦት ሰጥቶ እንዲያጠናክረው ካሳሰቡ በኋላ፣ ባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱም መግለጫ አውጥቶ ነበር፡፡ መግለጫ በወጣ በቀናት ውስጥ ግድፈቶችን የፈጸሙ የሚዲያ ተቋማትን የኮሙዩኒኬሽን ሚኒስትሩ አውግዘው በሕግ እንዲጠየቁ ከሚመለከተው አካል መነጋገራቸውን አስመልክቶ የሰጡትን መግለጫ አቶ ዘርዓይ ‹‹የግል አስተያየታቸው ነው። ቢሆንም አከብረዋለሁ፤›› ከማለታቸው ባለፈ፣ የሚዲያ ተቋማቱ ስህተት ቢፈጽሙም ከመቅጣት ይልቅ እንዲታረሙ ማገዝ የተሻለ ስለመሆኑ መናገራቸውን መዘገባችን ይታወሳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት ምሥረታ ከሁለት ዓመት በፊት ዕውን ሆኖ ሳለ፣ ለምን ወደ ሥራ እንዳልገባ ሚኒስትሩን ቋሚ ኮሚቴው ጠይቋል፡፡ ሚኒስትሩ በሰጡት ምላሽ የበጎ አድራጎትና ማኅበራት ኤጀንሲ ምክር ቤቱ በጋዜጠኞች ሳይሆን በሚዲያ ባለቤቶች የተቋቋመ በመሆኑ፣ ለመመዝገብ ሕግ አይፈቅድም በማለቱ ሳይመዘገብ እንደቀረ ገልጸዋል፡፡ ምክር ቤቱ ጠቃሚ በመሆኑ ችግሩ እንዲፈታ ፓርላማው ድጋፍ እንዲያደርግ ጠይቀዋል፡፡

Source:Reporter

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

Ministiroota Itiyoophiyaa har'a muudaman

Ibsa Dhaabbatummaa Dh.D.U.O

Obbo Muktaar Kadir pireezidaantii Mootummaa Naannoo Oromiyaa ta’uun lammata filataman