የሰላም ጉዳይ ሀገራዊ አጀንዳ መሆን አለበት አሉ የኦሮሚያ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳ

የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳ በዛሬው እለት ከሀይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና ምሁራን ጋር በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርገዋል።
በውይይቱ ወቅትም ርእሰ መስተዳደር አቶ ለማ መገርሳ የሀገሪቱ ሰላም ችግር ውስጥ መሆኑን አንሸሽግም፤ የሰላምን ጉዳይ ከእንጀራና ዳቦ በላይ አድርገን መመልከት ያስፈጋል ብለዋል።
ሰርቶ ለመኖርም ሆነ ለማስተዳደር ሰላም ወሳኝ ነው ያሉት አቶ ለማ፥ የሰላም ጉዳይ ለሀይማኖት አባቶች፣ አባ ገዳዎች ወይም ፖለቲከኞች ብቻ የሚተው የቤት ስራ አይደለም ሲሉም ተናግረዋል።

ስለዚህ ሁሉም በጋራ በመሆን በሰላም ጉዳይ ላይ ሊሰራ እንደሚገባም ነው ርእሰ መስተዳደር አቶ ለማ መገርሳ ያስረዱት።
የሀገሪቱን ሰላም ለማስጠበቅ የሰላም እጦት ችግሮችን በሚገባ ማጥናት እንደሚያስፈልገም ተናግረዋል።
አቶ ለማ አክለውም አሁን አሁን ኢትዮጵያውያን ተሳስበን ነው ወይስ በግድ ነው አብረን የምንኖረው የሚለውንም መመልከት ያስፈልጋል ብለዋል።
ኢትዮጵያዊ ዜጋ በሀገር ውስጥ በነፃነት መዘዋወር እና ሀብት ማፍራት ካልቻለ ጉዳዩ አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን መመልከት እንደሚያስፈዕግም ተናግረዋል።
ሀገር የግለሰቦች ስብስብ ነው ያሉት አቶ ለማ፥ የሀገር አንድነትና ሰላም ጉዳይ ደግሞ ለድርድር የሚቀርብ አይደለም ብለዋል።
የሀገሪቱን ሰላም ለማስጠበቅ እና የተጀመረውን የለውጥ ጉዞ ለማስቀጠልም እንደዚህ ብታደርጉ ከሚለው ሀሳብ ይልቅ እንዲህ ብናደርግ ማለት ይገባል ሲሉም ተናግረዋል።
የሀይማኖት አባቶችም የቤት እምነታቸውን አስተምህሮ በተገቢው መንገድ በማስተማር በመንግስትም ሆነ በማህበረሰቡ ላይ ገንቢ ተጽእኖ በመፍጠር ለውጥ እንዲመጣ መስራት እንደሚጠበቅባቸውም ገልፀዋል።
ከርእሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳ ጋር በሀገሪቱ ሰላም ዙሪያ የተወያዩት የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሀይማኖት አባቶች እና ምሁራን በበኩላቸው፥ ሰላምና እርቅ በውይይትና በቃላት ብቻ አይመጣም ምሳሌ መሆንም ይጠይቃል ብለዋል።
የሀገርን አንድነትና ሰላም ለማስጠበቅም የድርሻቸውን እንደሚወጡ አስታውቀዋል።
በሁሉም መንገድ መንግስት ትእግስት ማሳየቱ ጥሩ ሆኖ ሳለ ነገር ግን በአንድነትና አስተሳስሮ ያኖረን ህግ እና ስርዓት መከበር እንዳለበት በመግለጽ፤ መንግስትም ይህንን ሀላፊነቱን መወጣት እንዳለበት ተናግረዋል።
ርእሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳም፥ የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት የሀገርን አንድነት እና ሰላም ለማስጠበቅ በባለቤትነት ለመስራት ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

Ministiroota Itiyoophiyaa har'a muudaman

Ibsa Dhaabbatummaa Dh.D.U.O

Obbo Muktaar Kadir pireezidaantii Mootummaa Naannoo Oromiyaa ta’uun lammata filataman