“VOA”መሰረቱን ያጣ ሚዲያ


የአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ ቪኦኤ(VOA) የአማርኛ የኦሮሚኛና ትግርኛው ክፍል መሰረቱን ያጣ ሚዲያ ሆኗል።ይህ ሚዲያ ሰሞኑን ‘ለጥያቄዎ መልስ’ በሚል ፕሮግራሙ ላይ በአማርኛ አቶ ኒአሚን ዘለቀ የተባለ የአርበኞችና ግንቦት ሰባት ባለስልጣንን አቅርቦ ሲያነጋግር ነበር።

በዚህ ፕሮግራም የቪኦኤ የአማርኛው ክፍል ጋዜጠኞችን በይበልጥ ትዝብት ላይ የሚጥል ፕሮግራም ለአየር በቃ።

ሰውዬው በጣቢያው ላይ እንዲቀርቡ የተፈለገው የትህዴን ሊቀመንበር አቶ ሞላ አስገዶም ሻቢያን ክደው የአገራቸውን ልማትና እድገት ወደው  ከቡድናቸው ጋር በቅርቡ ወደ አገራቸው መመለሳቸውን ምክንያት በማድረግ ነው።

የአርበኞችና ግንቦት ሰባት ባለስልጣን አቶ ኒአሚን ዘለቀ ከአድማጭ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ትክክለኛውን ምላሽ ከመስጠት አድበስብሰው ማለፍን ነው የመረጡት።በየመሃሉ የተለያዩ ጥየቄዎችን የምታቀርብላቸው የቪኦኤ ጋዜጠኛም አጠያየቋ ለይምሰል እንጂ ሃቁን ለማውጣት እንዳልሆነ አድማጭ ያውቀዋል።ቪኦኤ እስከ አሁን አቶ ሞላ አስገዶምን ለምን ማነጋገር ሳይችል ቀረ?ነገሩ ግልፅ ነው አቶ ሞላ ቢቀርቡም የሚናገሩት የቪኦኤ ጋዜጠኞችና የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ከሚፈልጉት አቅጣጫ ውጭ ያለውን ነገር ነው።

እውነት ነው ቪኦኤ በአሜሪካ መንግስት የገንዘብ ድጋፍ ለበርካታ አመታት ለኢትዮጵያዊያን ተአማኒ ሚዲያ በመሆን እንደ አማራጭ ተወስዶ ሲያገለግል ቆይቷል።ከቅርብ አመታት ወዲህ ግን ይህ ሚዲያ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መሳሪያ ሆኖ በማገልገል ላይ ይገኛል።በዚህም የትምክህተኛና ጠባብ እንዲሁም የአክራሪ ሃይሎች መጠቀሚያ ሆኖ በማገልገል ላይ እንደሚገኝ በስራዎቹ በይፋ አስመስክሯል።

የአማርኛው ክፍል ብዙውን ጊዜ የኢትዮጵያን ጉዳይ በተመለከተ የሚያነጋግረው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ኢህአዴግ የሚመራውን መንግስት በመቃወም በውጭ አገራት የተሸሸጉ ምሁራን ተብዬዎችን ነው።በእርግጥ በአንዳንድ የጣቢያው ፕሮግራሞች ላይ መልካም አመለካከት ያላቸው ባለሙያዎችም በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ቃለ መጠይቅ ይደረግላቸዋል።ይህ  ግን እምዛም ነው።ሰፊውን የአየር ሰዓት እየወሰደ ያለው ጉዳይ የአሁኑን የኢትዮጵያ ስርዓት አፈር ድሜ ለማስበላት አልሞ የሚሰራው እንደሆነ ለማረጋገጥ ምንም ጥናት ማድረግ ሳያስፈልግ በጣቢያው በየእለቱ ከዜና ጀምሮ የሚሰራጩ ፕሮግራሞችን ብቻ መከታተልና ማድመጥ በቂ ነው።


የኦሮሚኛው ክፍልም በተመሳሳይ ሁኔታ የጠባብ ሃይል ዋነኛ መሳሪያ ሆኖ በማገልገል ላይ እንደሚገኝ በቋንቋው የእነ ኦነግ ባለስለጣናትን ቃለ መጠይቅ ብቻ ማድመጥ ከበቂ በላይ ነው።ከኦነግ ወጥቼ ሌላ ድርጅት አቋቁሜ በመንቀሳቀስ ላይ ነኝ ያሉት አቶ ሌንጮ ለታም በዚህ ክፍል ጋዜጠኞች በዋነኛነት ቃለ መጠይቅ የሚደረግላቸው ሰው ናቸው።ብዙ ቡድን ሆኖ የተበጣጠሰው የጠባቦች አለቃ የኦነግ አመራሮችም ‘የወያኔን መንግስት’ ለመስደብ ነሸጥ ሲያደርጋቸው ቃለ መጠይቅ ይሰጣሉ ወይም የክፍሉ ጋዜጠኞች አፈላልገው ቃለ መጠይቅ ያደርጉላቸዋል።

ለዚህ በዋነኛነት የአዲስ አበባና ፊንፊኔ ዙሪያ የኦሮሚያ ልዩ ዞን የጋራ ልማት እቅድን (እነርሱ ማስተር ፕላን ይሉታል) እስከ አሁን በስመ ቃለ መጠይቅ የተለያዩና በጠባብ አመለካከት የተካኑ ሰዎች የሚያወሩበትና እያመነዥኩ መሆናቸውን ማንሳት ይቻላል።

የጣቢያው ትግርኛ  ክፍልም የአረና ትግራይ ሊቀመንበር የእነ ገብሩ አስራት ዋነኛ ሚዲያ ሆኖ በማገልገል ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል።

እዚህ ላይ በመዋነኛነት መነሳት ያለባቸው ጥያቄዎች የቪኦኤ  ጋዜጠኞች የአማርኛ የኦሮሚኛና የትግርኛ ክፍል ጋዜጠኞች ለትውልድ አገራቸው ኢትዮጵያ ጠላት ሆነው ሌት ተቀን እንዲሰሩ ያደረጋቸው ጉዳይ ምንድነው? የሚለው ነው።

በእኔ እይታ እነዚሀ ሰዎች ‘እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል’እንዳለችው እንስሳ ከሆኑ ሰነባብተዋል።እነርሱ  በተለያየ ወቅት ከአገር ውጥተው በጥሩ ደመወዝ ተቀጥረው የዴሞክራሲ ባህል ያበበባት ናት በምትባለው አገረ አሜሪካ ሆነው በያዙት የሚዲያ መሳሪያ ተጠቅመው የትምክህት፤ የጠባብና የአክራሪ ሃይሎችን መርዝ ወደ ኢትዮጵያችን እየረጩ ነው።ይህን እንዲያደርጉ ያስገደዳቸው በርካታ ነገር እንዳለ ደግሞ መገመት ይቻላል።አንባቢ ብዙ ነገር ያውቃልና እስኪ እናንተው ድረሱበት።

ከኢትዮጵያ መንግስት ምን ይጠበቃል?

የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት በተለይም የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጽህፈት ቤት ሓለፊዎች ቪኦኤን ጨምሮ በሌሎች አለም አቀፍ ሚዲያዎች የኢትዮጵያን ገፅታ ሆነ ብለው የሚያበላሹ ጉዳዮች ሲሰራጩ ዝም ብለው ማለፍ አይጠበቅባቸውም።በእርግጥ ፀረ ኢትዮጵያ የሆኑ ጋዜጠኞች ከምንም ተነስተው የኢትዮጵያን ስም የሚያጎድፍ ስራ በሰሩ ቁጥር ማስተባበያ መስጠት አያስፈልግም፤ተገቢም አይደለም።ምክንያቱም አድማጭም የራሱን ድምዳሜ የሚሰጥባቸው ጉዳዮች እጅግ በርካታ ናቸውና።


ነገር ግን እጅግ ወሳኝ በሆኑ አገራዊና ክልላዊ ጉዳዮች ላይ የማስተባበያ መግለጫዎችን በማውጣት እንዲሁም በራሳቸው ሚዲያ ቪኦኤ ላይም በመቅረብ ተገቢውን ምላሽ መስጠት የግድ ነው።ምንም አያመጡም በሚል አስተሳሰብ በዝምታ ማለፍ አያስፈልግም ተገቢም አይደለም፤እንዲሁም ሃላፊነትን አለመወጣት ስለሆነ አንድ ቀን ማስጠየቁ አይቀርም።ስለዚህ የዘርፉ ሃላፊዎች ከምን ቸገረኝና ምንም አይመጣም አስተሳሰብ ወጥተው የስራ ድርሻቸውን በመወጣት የአገር አጥፊ ሚዲያዎችን አሉባልታና ፕሮፓጋንዳ እርቃን የሚያስቀር ትክክለኛ መረጃ መስጠት ይጠበቅባቸዋል።
 




አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

Ministiroota Itiyoophiyaa har'a muudaman

Ibsa Dhaabbatummaa Dh.D.U.O

Obbo Muktaar Kadir pireezidaantii Mootummaa Naannoo Oromiyaa ta’uun lammata filataman