"ከሐሰተኛ የዲጂታል ወያኔ የማኅበራዊ ትሥሥር ገፆች ተጠንቀቁ" - ኢመደአ

 




ዲጂታል ወያኔ ሕዝብን ከሕዝብ የማጋጨት እና ሀገርን የማተራመስ ተግባሩን የቀጠለ በመሆኑ ኅብረተሰቡ ኮርኳሪ መልዕክቶችን ተጠቅመው የጥፋት ተልዕኮ ይዘው ከሚመጡ ሐሰተኛ የማኅበራዊ ትሥሥር ገፆች ሊጠነቀቅ እንደሚገባ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር አሳሰበ።
ዲጂታል ወያኔ ከአካላዊ ጦርነቱ አስቀድሞ ኢትዮጵያውያንን ለማባላት፣ ለማጋጨት እና እኩይ ተግባሩን ለማስፈፀም የተለያዩ ትርክቶችን እየፈጠረ እኩይ ተግባራትን ሲያከናውን የቆየ እና አሁንም በዚህ ተግባሩ እንደገፋበት የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ሹመቴ ይግዛው ገልጸዋል።
እንደ ዶ/ር ሹመቴ ገለጻ፣ ባለፉት 30 ዓመታት የተሠሩ የፖለቲካ ትርክቶች እና ሴራዎች ለማኅበራዊ ትሥሥር ገፆች ትልቅ ግብዓት ወደ መሆን አዝማሚያ ሄደዋል።
ይህንን አጋጣሚ በመጠቀም አሸባሪው ሕወሓትን ጨምሮ በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ወጪ ያሉ የኢትዮጵያን መልካም ነገር የማይፈልጉ አካላት በዲጂታል መንገድም ሆነ በአካላዊ ጦርነት ኢትዮጵያን ለማጥቃት ያላሰለሰ ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ።
ዲጂታል ወያኔ የዲጂታል ጦርነቱን በተለያየ መንገድ እየተገበረ መሆኑን ገልጸው፣ ለአብነትም ኦሮሞ ሳይሆኑ የኦሮሞ ስም ገፆችን በመክፈት፣ አማራ ሳይሆኑ የአማራ ስም የያዘ ገፅ በመክፈት የብሔር ጉዳዮችን አንስቶ በመሳደብ እና ተቆርቋሪ በመምሰል በሐሰተኛ ገፅ ተጠቅመው ከፍተኛ የሆነ የመረጃ ማዛባት ጦርነት እያካሄዱ ነው ብለዋል።
ከ800 ሺህ በላይ ሐሰተኛ ማኅበራዊ የትሥሥር ገፆች ተከፍተው ሀገርን ለማተራመስ እየሠሩ ስለመሆኑም ጠቅሰዋል።
ቁጥራቸው በርከት ያለ የሐሰተኛ መረጃ አሠራጮች እና የሐሰተኛ ገፅ ተጠቃሚዎች በክስ ሂደት ላይ እንዳሉ ተነግሯል።
ዋናው ነገር ከገበያ የተገኘ ሁሉ እንደማይገዛ እንዲሁ መረጃዎች ሁሉ አይገበዩም፤ ምንጫቸው መጣራት ይኖርበታል።
በማኅበረሰቡ ዘንድ የማኅበራዊ ዲጂታል ሚዲያዎችን በአግባቡ የመጠቀም ግንዛቤ እምብዛም መሆኑ ለሚነሣው ሐሰተኛ መረጃ ጥሩ አጋጣሚ እንደፈጠረለት ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
በመሆኑም ግንዛቤ ከማስጨበጥ ሥራው ጎን ለጎን ሐሰተኛ መረጃ የሚያሠራጩ የማኅበራዊ ትሥሥር ገፆችን ማዘጋት እና በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ሥራዎች እየተሠሩ እንደሆነም መግለጻቸውን ኢፕድ ዘግቧል።
ሐሰተኛ የማኅበራዊ ትሥሥር ገፆች ዋና ዓላማ ለግለሰብ የግል ፍላጎት፣ ፖለቲካዊ ጥቅምን ለማስጠበቅ አሊያም ማኅበራዊ ጉዳዮች ጋር የተያያዘ ተገቢ ባልሆነ መንገድ ፍላጎትን ማስፈፀም በመሆኑ በጥፋታቸው ልክ ተጠያቂ መደረግ ይገባቸዋል ብለዋል ዶ/ር ሹመቴ።
ለአብነት ፌስቡክን 1.3 ቢሊየን ሐሰተኛ አካውንቶችን በ2021 (እ.አ.አ) መጨረሻ ላይ ማጥፋቱ እና በ2022ም ይህ የሚቀጥል ይሆናል ተብሎ ስለሚጠበቅ ኢትዮጵያ በዘርፉ የምታደርገውን ትግል እንደሚያጠናክርላት ተስፋ እንደተጣለበት ጠቅሰዋል።

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

Ministiroota Itiyoophiyaa har'a muudaman

Ibsa Dhaabbatummaa Dh.D.U.O

Obbo Muktaar Kadir pireezidaantii Mootummaa Naannoo Oromiyaa ta’uun lammata filataman