የህዝቦች የመዋደድና ተቻችሎ አብሮ የመኖር ባህል ተጠናክሮ ይቀጥላል!!

ከኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ኮሙኒኬሽን ቢሮ የተሰጠ መግለጫ

በሀገራችንና በክልላችን ውስጥ ባላፉት የዘውዳዊና አንባገነናዊ ስርአቶች ከሚከተሉት አመለካከት የመነጨና የተሳሳተ ፖሊሲና ስትራቴጂ ስራ ላይ በማዋል ህዝቡ ሰብዓዊና ዴሞኪራሲያዊ መብቱ ተነፍጎ ለከፋ ችግርና ሰቆቃ ተዳርጎ ሲሰቃይ ቆይቷል፡፡


ሀገራችን የብዙ ብሄር ብሄረሰቦች መነኀሪያና የተለያዩ እምነት የሚያራምዱ ዜጎች የሚኖሩባት ሀገር መሆኗ እየታወቀ ሲወራረስ በመጣ ዘውዳዊ ስርአት ተጭነውት ይህንን ማንነትና ብዝሀነት በማፈን ህዝቡን ለተለያዩ መከራዎች  በመዳረግ ሲገዙት ቆይተዋል፡፡

እነኚህ አንባገነኖች አንድ ሀገር፤ አንድ ህዝብ አንድ ባህል፤ አንድ ኃይማኖትና አንድ ታሪክ በሚል ፍልስፍና ህዝቡን በሀይል በማስገበራቸውና በመግዛታቸው  ሃገራችን ለድህነት፣ ለመሀይምነትና ለኋላቀርነት እንድትጋለጥ በማድረግ የሀገራችን መልካም ስምና ገጽታ በሚያሳፍር ረሀብ፤ድህነትና ኋላቀርነት እንዲታወቅ አድርገው ነበር፡፡

ባሳለፍናቸው ሁለት አስርት አመታት ዉስጥ የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞኪራሲያዊ መብቶች ያለአንዳች ገደብ ሊከበር ችሏል፡፡  የሀገራችን የድህነት፣ የመሀይምነትና የኋላቀርነት ታሪክ ተቀይሯል፡፡  በህዝቡና በመንግስት ቅንጅት በተሰሩ ስራዎች ሁሉን አቀፍ ሁለንተናዊ ልማት በመመዝገቡ ይህች ሀገር የምትታወቅበት የድህነት ተራራ መናድ ጀምሯል፡፡

በሀገራችን ብዙ ብሄሮች ብሄረሰቦችና የተለያዩ እምነት የሚያራምዱ ዜጎች የሚኖሩባት ሲሆን በሀገራችን ታሪክ ረጅም እድሜ ባስቆጠረው አብሮነታቸው እያዳበሩ በመጡት የመከባበር፤ የመቻቻል፤ የመፈቃቀርና የመረዳዳት እሴት በሀገር ጉዳይ ላይ በአንድነት በመቆም በልማት፤ በዴሞክራሲዊ ስርአት ግንባታና በሀገር ሰላም ማስከበር ላይ በአንድነት በመቆም የህዝብን ጥቅምና የሀገርን እድገት በማይመኙ ኃይሎች ለተለያየ ፈተና ሲዳረግ መቆየቱ ይታወሳል፡፡

ህዝባችን የዜጎች የዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶች መከበር በህገ-መንግስቱ ዋስትና ካገኘ በኋላ ትኩረቱን የድህነትን ተራራ ወደ መናድ አድርጎ ፈጣን ልማትና ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ እድገት በማስመዝገብ በየደረጃው ተጠቃሚ መሆኑ ቀጥሏል፡፡

ህዝባችን በሚያደርገው ትግልና እያጣጣመ ባለው የልማት ውጤት ሁልጊዜ ፈተና ሳያጋጥመው ቀርቶ አያውቅም፡፡ የጠባብነትና የትምክህተኝነት አባዜ የተጠናወታቸው ኃይሎች  የተለያዩ አጀንዳ  ተገን በማድረግ ከጥፋት ተግባር የሀገራችንን ደህንነትና የህዝባችንን ሰላም ሲፈታተኑት ቆይተዋል፡፡ የልማት፤ የዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታና ዘላቂ ሰላም የማስፈን ፕሮግራሞችን ተግባራዊ ለማድረግ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉ እንቅፋት ለመሆን ያልሞከሩበትና ያልተሯሯጡበት ጊዜ አልነበረም፡፡

በዚህ አመት እነዚህ የጥፋት ኃይሎች በክልላችን አንዳንድ ቦታዎች በተፈጠሩ ችግሮች በሰው ነፍስና በንብረት ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡ ልማታዊ ስርአታችንን ለመናድና ህዝቡን ወደ ዳግም ባርነት ለመክተት ያደረጉት ጥረት በህዝቡ ሙሉ ተሳትፎ ከሽፎ መረጋጋት ተፈጥሮ ሁሉም ነገሮች ወደ ቀድሞ ቦታቸው ተመልሰው ህዝቡም ወደ ልማት ስራው ተመልሷል፡፡

ይሁን እንጂ እነኚህ የጥፋት ኃይሎች ይዘትና ዘዴዎችን በመቀያየር የጥፋት ተግባራቸውን ከመፈጸም አልተቆጠቡም፡፡ በነዚህ የጥፋት ኃይሎች በሚፈጸመው የጥፋት ስራ ውስጥ በዚህ ሰሞን የኃይማኖትና የብሄር ግጭት እምነትን ከእምነት፤ ብሄርን ከብሄር የሚያጋጭ አጀንዳ ለመጠቀም እየተሯሯጡ እንዳሉ ተጨባጭ የሆነ ምልክት ይታያል፡፡ በምዕራብ አርሲ ዞን በተወሰኑ ወረዳዎች ውስጥ በፈጠሩት ሁከት በሰው ህይወትና በንብረት ላይ ጉዳት ደርሷል፤ ከምንም በላይ የኃይማኖት ተቋማትን ማቃጠላቸው የኃይማኖቶችና የብሄር ብሄረሰቦች ተከባበሮና ተዋዶ መኖር ላይ የጥፋት ዘመቻ ለማድረግ ማቀዳቸውን ያጋለጠ ሆኗል፡፡

ለዘመናት በመከባበርና በአብሮነት በኖረው ህዝብ መካከል ያልተገባ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት እምነትን ተገን በማድረግ መንቀሳቀስ ለህዝብ ካለቸው ንቀት የሚመነጭ ነው፡፡ የእነዚህ ኃይሎች የህዝባችን ተጠቃሚነት መጨመርና የልማታችን መፋጠን ለማዳከምና ለመግታት መሯሯጥ የተስፋ መቁረጣቸው ማረጋገጫ መሆኑ የማይታበል ሀቅ ነው፡፡    
       
ህዝባችን አብሮ መኖር እሴት ያለው የተከበረና ነውርን የሚያውቅ ስለሆነ በጠባቦችና በትምክህተኞች አመለካከት የሚወናበድ አይደለም፡፡ እነዚህ ኃይሎች በፈጠሩት ሁከት በጠፋው የፀጥታ  ሀይሎች ህይወት የንብረት ውድመትን ህዝቡ በጋራ ወጥቶ ከማውገዝም በላይ ሁከቱ በቁጥጥር ስር እንዲውል አድርጎታል፡፡  ስለዚህ ከዚህ ቀደም እንደሚያደርገው የጥፋት ኃይሎችን ፊት ለፊት በመጋፈጥ ሴራቸውን በማጋለጥ ከመንግስት ጎን በመሰለፍ ሰላን ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡   


አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

Ministiroota Itiyoophiyaa har'a muudaman

Ibsa Dhaabbatummaa Dh.D.U.O

Obbo Muktaar Kadir pireezidaantii Mootummaa Naannoo Oromiyaa ta’uun lammata filataman